ዶ/ር ማማሩ አያሌዉ ሞገስ
የአብክመ ዉሃ፣መስኖና ኢነርጂ ልማት ቢሮ ሃላፊ
የአማራ ብሄራዊ ክልላዊ መንግስት ውሃ፣ መስኖና ኢነርጂ ልማት ቢሮ የክልሉን የውሃ ሃብት ማስተዳደር፣ ንጹህ የመጠጥ ውሃ ማቅረብ፣ ከአነስተኛ እስከ መካከለኛ ደረጃ ያሉ የመስኖ አውታሮችን በመገንባት ለተጠቃሚው ህብረተሰብ ማስተላለፍና የአማራጭ ኢነርጂ ቴክኖሎጂዎችን በማስተዋወቅና በማቅረብ ህብረተሰቡን ተጠቃሚ ማድረግ ከክልሉ መንግስት የተሰጠው ተግባርና ሃላፊነት በመሆኑ ይህን ተግባርና ኃላፊነት ለመወጣት የሚያስችል ሰፊ ስራ እየሰራ ይገኛል፡፡
በሁለተኛዉ የእድገትና ትራንስፎርሜሽን ዕቅድ ዘመን የመጠጥ ውሃ አቅርቦት ሽፋን በገጠር ሁሉም አርሶ አደር ከሚኖርበት አካባቢ ከ1 ኪ/ሜ በላይ ሳይጓዝ 25 ሊትር ዉሃ በቀን ለእያንዳንዱ ሰው፤ በከተማ የህዝብ ቁጥራቸዉ ከ20,000 እስከ 999,999 ህዝብ ለሚኖርባቸዉ የክልላችን ከተሞች ከ50 እስከ 80 ሊትር ዉሃ በቀን ለሰዉ ለማዳረስና የህዝብ ቁጥራቸዉ ከ20,000 በታች ለሆኑ የክልላችን ከተሞች በ250 ሜትር ርቀት 40 ሊትር ዉሃ በቀን ለሰዉ ለማድረስ የተቀመጠዉን አዲስ ስታንዳርድ መሰረት በማድረግ የተጣለዉን ግብ ለማሳካት ሰፊ ርብርብ በማድረግ ላይ ይገኛል፡፡
በዚህም መሰረት ከላይ በተቀመጠዉ ስታንዳርድ በዕትዕ-2 መጀመሪያ የንጹህ መጠጥ ዉሃ ሽፋናችን በገጠር 53.46% በከተማ 54% እንደ ክልል 53.54% ላይ የደረሰ ሲሆን ከዚህ በመነሳት በአምስት ዓመት የተቀመጠዉን ግብ ለማሳካት ከፍተኛ ስራ ተሰርቶ በከተማም ሆነ በገጠር የንጹህ መጠጥ ዉሃ ሽፋኑን ከፍ ማድረግ ተችሏል፡፡